Sunday 15 October 2017

ለኢትዮጵያ የመከላከያና ፓሊስ ሠራዊት አባላት የተደረገ ጥሪ

ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ የአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር
በድጋሚ የቀረበ

የተከበራችሁ የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አባላት፤ የፌደራልና የክልል ፓሊስ አባላት፤ የአጋዚ ልዩ ኮማንዶ ጦር አባላትና ሌሎች የሥርዓቱ ታጣቂዎች። አገራችን በለውጥ ሂደት ውስጥ ባለችበት በዚህ ወሳኝ ወቅት ለእናንተ ቀጥታ መልዕክት ማስተላለፍ የሚገባ ሆኖ ስላገኘሁት ይህንን አጭር መልዕክቴን በጥሞና እንድታዳምጡኝ፤ የሰማችሁ ላልሰሙት እንድታደርሱልኝ እጠይቃለሁ።

የአገር መከላከያ ሠራዊት አባል መሆን ከፍተኛ ክብር ያለው ሙያ እንደነበር የምታውቁት ነው። ለሀገር ዘብ መቆም መልካም ዜጎች ሁሉ የሚመኙት ተግባር ነው። አንድ ሰው ቃለ መሀላ ፈጽሞ የመከላከያ ሠራዊት ዩኒፎርም ከለበሰ በኋላ ተራ ዜጋ አይደለም። አገሪቷ በዜጎቿ ማየት የምትፈልጋቸውን መልካም እሴቶችን ሁሉ በወታደሮቿ ማየት ትሻለች፤ ለሕዝብ ተቆርቋሪነት፣ ሀገር ወዳድነት፣ ፍትሀዊነት፣ ጀግንነት፣ ታማኝነት በወታደሮቿ ማየት ትሻለች። ለዚህም ነው በብዙ አገሮች ውስጥ ያሉ ሕፃናት “ስታድጉ ምን መሆን ትፈልጋላችሁ?” ሲባሉ ከሚሰጧቸው መልሶች ግንባር ቀደሙ “ወታደር” የሚሆነው። በሀገራችንም ዘመናዊ ጦር ከመደራጀቱ በፊት አያት ቅድም አያቶቻችን ራሳቸውን በወታደርነት አሰልጥነው፤ ወራሪ ሲመጣ በየጎበዝ አለቆቻቸው እየተቧደኑ ዘመናዊ ጦሮችን ሳይቀር ተዋግተው በማሸነፍ የአገራችንን ሉዓላዊነት አቆይተውልናል። ዘመናዊ ጦር ከተደራጀ ወዲህም እስከ ህወሓት አገዛዝ የነበሩ አስተዳደሮች ብዙ እንከኖች ቢኖርባቸውም እንኳን የመከላከያ ሠራዊትን የአገር መከላከያ ሠራዊት አድርገውት ቆይተዋል። የሠራዊቱን ክብርና ሞገስ ለመጠበቅም የተቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል። ይህ ጥረት ግን በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ሙሉ በሙሉ ተቀልብሷል።

የፓሊስ ሠራዊት ሥራ ለሕዝብ የዕለት ተዕለት ኑሮ ዋስትና መስጠት ነው። ዜጎች በሰላም ከቤታቸው ወጥተው በሰላም የመመለሳቸው ዋስትና ከወገናቸው ከፓሊስ ሊያገኙ ይሻሉ። ሕዝባዊ ፓሊስ የወሮበሎች፣ የሌቦችና የማጅራት መቺዎች ጠር፤ የድሆችና ደካሞች አጋር ነው። ሕዝባዊ ፓሊስ የፍትህ ጠበቃ ነው። እንዲህ ዓይነቱን ፓሊስ በህወሓት የአገዛዝ ዘመን ማየት አልቻልንም።

የህወሓት አገዛዝ የተከበሩትን የውትድርናና የፓሊስ ሙያዎችን አዋርዶ ለሀገርና ሕዝብ ደህንነት ሳይሆን ለአንድ ቡድን ሥልጣን መከበር የቆሙ ኃይሎች እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። አሁን ያለው የኢትዮጵያ መከላከያና የፓሊስ ሠራዊትን ስናስብ በአዕምሮዓችን የሚመጡት የሚከተሉት ሀቆች ናቸው።

የጦር ሠራዊቱ፣ ብቃትና ዕውቀት እንዲሁም የሀገር ፍቅር ባላቸው ጄኔራሎችና የጦር መኮንኖች የሚመራ ሳይሆን በተቃራኒው ምንም ዓይነት ወታደራዊ ትምህርት በሌላቸው ከሽምቅ ውጊያ ቡድን አዛዥነት ወደ ዘመናዊና መደበኛ ጦር አዛዥነት በድንገት ያደጉ፤ ራሳቸውን ከዘመናዊ ሠራዊት አደረጃጀትና አመራር ጋር ያላዋሃዱ፤ ከሀገር ጥቅም ይልቅ የራሳቸው የግል ጥቅም የሚበልጥባቸው፤ የማይጠረቁ ስግብግቦች፤ ታማኝነታቸው ለሀገር ሳይሆን አባል ለሆኑባቸው ፓርቲዎች የሆኑ ግለሰቦች ናቸው።

ዛሬ ያለው የኢትዮጵያ ሠራዊት በወያኔየስለላ መረብ ተተብትቦ ወይም በእነርሱ ቋንቋ “ተጠርንፎ” በግድ የተያዘ እንደቁም እስረኛ ሊቆጠር የሚችል በከፍተኛ ምሬትና በደል ውስጥ የሚገኝ ሠራዊት መሆኑን እናውቃለን። የሠራዊቱን ክብር በሚነካ፤ ስብዕናን በሚያዋርዱ ዘለፋዎችና በግምገማናላው እንዲዞር፣ ሞራሉ እንዲላሽቅ የተደረገ ሠራዊት ነው። የህወሓት ጄኔራሎችና ካድሬዎች የሚያወርዱበት ዘለፋና ስድብ የዕለትተዕለት ቀለቡ የሆነ፤ ሞራሉም የላሸቀ ሠራዊት ነው።

አንድ ተራ የህወሓት ካድሬ ወይንም የበታች ሹም የዘረኛው ሥርዓት በሚሰጠው ልዩ ግምትና ስልጣን ከሌሎች ብሔሮችና ብሔረሰቦች የመጡ በማዕረግም በዕውቀትም የበላይ የሆኑንትን ሻለቆችና ኮሎኔሎችን የሚያንጓጥጡበት፣ የሚያዋርዱበትና የሚያሸማቅቁበት፤ አመራሩበወታደራዊእዝና ወታደራዊ ስነምግባር መሠረት የሚመራሳይሆንበብሄር የበላይነት ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ዲሲፕሊንና ውህደት የሌለው ሠራዊት ነው። በብሔር የተከፋፈለ በመሆኑ በውስጡ ያለው ጓዳዊ ስሜት በእጅጉ የላላ ሠራዊት ነው።

የፍትህ ጥያቄየሚያነሱ የሠራዊቱ አባላት ለህወሓት ካድሬዎች ስላልጣማቸው ብቻ ያለ ወታደራዊ ህግና አግባብበ አንድ የህወሓት ካድሬ ትዕዛዝ ብቻ ደብዛቸው ሊጠፋ እንደሚችል ስለሚያውቁበከፍተኛ የፍርሃት እና በራሳቸው ላይ እምነት እንዲያጡ የተደረጉ ናቸው።
ይህ ሠራዊት ለወያኔ ጠባብ አጀንዳ በየግንባሩ ዘመቻ እንዲሄድ ሲገደድና ሲማገድ የህወሓት ካድሬዎችና ጄኔራሎች የሕይወትና የደም ግብር እንዳይከፍሉ ከአደጋ እንዲጠበቁ የሚደረግበት ዘዴና ስልት የተቀየሰበት የዘረኝነትና የአድሎ ሥርዓት ውስጥ የተጣደ ሠራዊት ነው።
ሠራዊቱ ሲቆስል፣ ደሙን ሲያፈስ፣ ፈንጂ ሲረግጥ፣ ሕይወቱን ሲገብር የህወሃትቅምጥል ጄኔራሎችና መኮንኖች ቅጥባጣ አስረሽ ምችው በየከተማው እንደሚባልጉ የሚያውቅ ሠራዊት ነው።

ጫማና የደንብ ልብስ ከዚያም አልፎ የሚበላዉን ምግብ ከሚከፈለዉ ትንሽዋ ደሞዙ ላይ እየተቆረጠበት እናት አባቱን ለመጦር እና ልጆችን ለማሳደግፈተና ውስጥ የሚገባ፤ ለበርካታ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የተዳረገ ሠራዊት ሆኖ ሳለ በአንፃሩ የህወሓት ጄኔራሎችና ከፍተኛ መኮንኖች በኮንትሮ ባንድ ንግድና በዘረፋ ሲከብሩ፤ ንግዳቸውን በግላጭ ሲያጧጥፉ፤ ባለብዙ ህንፃዎች ባለቤቶች በመሆን በዘመድ አዝማዶቻቸዉ ስም ጭምርሀብት ሲያካብቱ፤ የህዝቡን መሬት ያላግባብ ሲቀሙና ሲቀራመቱ፤ በሰላም አስከባሪ ኃይል ስም በተባበሩት መንግስታት በየሀገሩ እየተመደቡ በወር እስከ 25,000 የአሜሪካ ዶላር ተከፋይ ሆነው ሲቀማጠሉ በሚገባ እያስተዋለ የሚገኝ ሠራዊት ነው።

በተጨማሪም እንደው ድንገት ለምርጦቹ የሚደርሰው የሰላም ማስከበር ተሳትፎ ግዳጅ ሲሄድ ሊያግኝ ከሚገባው የኪስ ገንዘብ ላይ አብዛኛውን ለራሳቸዉ ጥቅም በማዋል እና ሀገሪቷ ከዚህ ከሰላም ማስከበር ልታገኝ የሚገባትን ጥቅማጥቅም በራሳቸዉ በህዉሃት ጄኔራሎችና አመራሮች የግል ኪስ በማስገባት ራሳቸውንና ዘመድ አዝማዶቻቸዉን እያበለጸጉበት ይገኛሉ።

ሠራዊቱ ከትንሿ ደመወዙ ለመለስፋዉንዴሽን፣ ለአባይግድብግንባታ፣ ለተለያዩ የተሃድሶ መዋጭዎች፣ ለአመት በአል ድግሶች መዋጮ እንዲፈል የሚገደድ ምስኪን ነው። አላዋጣም፤ ገንዘብ የለኝም ብሎ ቢል ጸረ ሰላም ወይንም ሌላ ስም ተሰጥቶት ለተለያዩ አይነት ቅጣቶች ይዳረጋል። ሕገ መንግሥቱ በግልጽ ቢከለክልም እንኳን በሰራዊቱ ውስጥ የድብቅ የሕወሀት አደረጃጀት ፈጥሮ በሰራዊቱ ውስጥ የልጅና የእንጀራ ልጅ ስሜት ፈጥሮ የሚከፋፍል እኩይ ኃይል ነው ይህን ሰራዊት የተቆጣጠረው።

በፌዴራል ፖሊስና በአጋዚ ልዩ ኮማንዶ ውስጥ ነግሶ የሚታየው ሁኔታ ከላይ ከዘረዘርናቸው የተለየ አይደለም። ሠራዊቱ የአዛዦቹ አገልጋይ በመሆን የበይ ተመልካች የሆነበት መዋቅር ነው። ሞት፣ የአካል መጉደልና ድህነት ለሠራዊቱ አባላት፤ በአንፃሩ ምቾችና ድሎት ግን ለአዛዦቹ እንዲሆን ታቅዶ የተደራጀ ሠራዊት ነው።

ኢትዮጵያ በየዘመኑ እያደገና እየዘመነ የመጣ ሞያን፣ ችሎታንና ወታደራዊ ሳይንስን አዳብሎ የታጠቀና ከተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የተዉጣጣ ዘመናዊ የአገር መከላከያ ተቋም የነበራት አገር ነበረች። ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች አዲስ አበባን ሲቆጣጠሩ ይህንን ዘመናዊ የአገርና የወገን መከታ የሆነዉን ሠራዊት አፍርሰዉና ለእናት አገሩ የተዋደቀዉን ሠራዊት ለማኝ አድርገዉት ነዉ በህወሓት የበላይነት የሚመራ አዲስ የመከላከያ ሠራዊት የገነቡት። ይህ ህወሓት የገነባዉ ሠራዊት በአደረጃጀቱም ሆነ በቀን ከቀን ስራዉ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅምና ፍላጎት ጋር በምንም መልኩ የተገናኘ አይደለም። ይህንን መከላከያ ሠራዊት የፈጠረዉ ህወሓት፣ የሚመራዉና የሚቆጣጠረዉ ህወሓት፤ ሠራዊቱ በሚወስዳቸዉ እርምጃዎች ሁሉ ዋነኛዉ ተጠቃሚም የህወሓት/ኢህአዴግ ጥቂትዘራፊ መሪዎች ብቻ ነዉ።

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ሆይ!

ህወሓት/ኢህአዴግ ለኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ የደገሰዉ የጥፋት ተልዕኮ ካልተሳካ አንተን እንደለመደዉ ሜዳ ላይ በትኖና ባንተ ትከሻ ላይ እንደመዥገር ተጣብቆ የዘረፈዉን የአገር ሀብትና ንብረት ይዞ አገር ለቅቆ እንደሚጠፋ ምንም ጥርጥር የለዉም። ለዚህ የሽሽት ጉዞዉ ደግሞ ለረጂም ግዜ ተዘጋጅቷል። በቢልዮኖ ዶላሮች የሚቆጠር ሀብት በውጭ ሀገሮች አስቀምጧል። በዚህሠራዊት ዉስጥ የአገሩን ዳር ድንበር የጠበቀ እየመሰለዉ የህወሓት መሳሪያ ሆኖ የራሱን ወገኖች ከሚገድለዉ ኢትዮጵያዊ ዉስጥ ከአስር ዘጠኙ የህወሓት/ኢህአዴግን መወገድ የሚናፍቅ ዜጋ ነዉ። ችግሩ ይህ ሠራዊት ልክ እንደ ሲቪል ወግኖቹ በዘርና በቋንቋ ተለያይቶ የተደራጀ በመሆኑ እርስ በርስ ተገናኝቶ መነጋገርና መወያየት አለመቻሉ ነው።

ይህ ሙሉ በሙሉ በህወሓት ቁጥጥር ስር የሚገኘዉ ሠራዊት ባለፉት ሀያ አምስት ዓመታት የወሰዳቸዉን ፀረ ሕዝብና ፀረ አገር እርምጃዎች አንድ በአንድ ስንመለከት ይህ ተቋም በሚወስዳቸዉ እርምጃዎች የሚጎዳዉ የሠራዊቱ ጡንቻ የሚያርፍበትን የኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የሠራዊቱ አባላት እራሳቸዉም የራሳቸዉ እርምጃ ሰለባዎች ናቸዉ። ታድያ ለምንድነዉ ይህ ሠራዊት ከ25 አመት በላይ እሱን እራሱን፣ እናቱን፣ አባቱን፣ እህቱንና ወንድሙን የሚጎዳ እርምጃ የሚወስደዉ? የአገርን ዳር ድንበር ከባዕዳን ወራሪዎች ለመከላከል የተደራጀና የታጠቀ መከላከያ ሠራዊት ለአዛዦቹ መታዘዝ እንዳለበት ከማንም የተሰወረ አይደለም። ሆኖም አንድ የአገሬን አንድነትና የወገኖቼን ደህንነት እጠብቃለሁ ብሎ ቃለ መሃላ የፈጸመ የመከላከያ ሠራዊት አባል ደህንነቱን መጠበቅ የሚገባዉን ሕዝብ በነጋና በጠባ ግደል ተብሎ ትዕዛዝ ሲሰጠዉ ትዕዛዙን ከመፈጸሙ በፊት ማንን ነዉ የምገድለዉ ለምንስ ነዉ የምገድለዉ ብሎ እራሱን መጠየቅ አለበት።

ዛሬ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዘመናዊ የባርነት አዋጅ ታዉጆበታል። ህወሓት ይህንን አዋጅ ተግባራዊ ለማድረግ የሚሯሯጠዉ አንተን ከሕዝብ አብራክ የወጣኸዉን የሕዝብ ልጅ በመጠቀም ነዉ። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትና የፖሊስ ሀይል ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነጻነትና እኩልነት ይዋጋል እንጂ እሱንና ወገኖቹን የህወሓት ባሪያ የሚያደርግን አዋጅ አያስፈጽምም። ይህ አገርንና ሕዝብን ለመጠበቅ ህገ መንግስታዊ አደራ የተሸከመ ሠራዊት የታጠቀዉን መሳሪያ ማዞር ያለበት በወንድሞቹና በእህቶቹ ላይ ሳይሆን ሠራዊቱንና ኢትዮጵያን በትኖ ለመጥፋት ዝግጅት እያደረገ ባለዉ በጠላቱ በህወሓት ጥቂት ዘራፊ የሲቪልና ወታደራዊ መሪዎችላይ ነዉ።

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አባላት ሆይ!

የኛ ፍላጎት ፍትህ፣ነፃነት፣ እኩልነትና ዲሞክራሲ የሰፉኑባት ኢትዮጵያ እዉን ሆና ማየት ነዉ። እርግጠኞች ነን የእናንተም ፍላጎት ከዚህ የተለየ አይደለም። እነዚህን እኛም አናንተም የምንፈልጋቸዉን እሴቶች ቀምቶን ሁለታችንንም እንደ ባሪያ ረግጦ የሚገዛን ዘረኛዉ የህወሓት/ኢህአዴግሥርዓት ነዉ። እናንተና እኛ ይህንን አንድ ላይ የሚረግጠንን ሥርዓት ጎን ለጎን ቆመን በጋራ መታገል ነዉ ያለብን እንጂ እርስ በርስ መተላለቅ የለብንም። ደግሞም ሁለት ፍትህ፣ ነፃነትና እኩልነት የናፈቃቸዉ ወንድማማቾች ነፃነታቸውን ቀምቶ የሚረግጣቸዉን ኃይል አንድ ላይ ሆነዉ ይፋለሙታል እንጂ እርስ በርስ አይተላለቁም። በዚህ የነጻነት ትግል ላይ የምንሳተፍ ወገኖችህ ወንድሞቻችንን በመግደል አናንተም እኛን ወንድሞቻችሁን በመግደል የሚገኝ ነገር ቢኖር ባርነትና የአገር አንድነት መፍረስ ብቻ ነዉ። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት አገሩንና ወገኖቹን የሚጠብቅ ኃይል ነዉ እንጂ ጠላቶቹ ግደል የሚል ትዕዛዝ በሰጡት ቁጥር በገዛ ወገኖቹ ላይ የሚተኩስ ኃይል አይደለም።

አንተ የኢትዮጵያ መለዮ ለባሽ ሆይ!

ዛሬ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በኮንሶ፣ በቤኒሻንጉልና ኦጋዴን ዉስጥ እህቶችህ “ወንድም ጋሼ” ድረስልን ብለዉ እየተጣሩ ነዉ፤ ወንድሞችህ “ጋሽዬ” አድነን እያሉህ ነዉ፤ አባትህና እናትህ “ልጄ አንተ እያለህ እንዴት እንዲህ ይደረጋል?” ብለዉ እየጮሁ ነዉ። መቼ ነዉ የምትደርስላቸዉ? መቼ ነዉ ከእስርና ከጥይት የምታድናቸዉ? መቼ ነዉ ተስፋ የምትሆናቸዉ?

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትና ፓሊስ አባላት ሆይ!

የህወሓት አገዛዝ ልትጠብቀው ከሚገባህ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ደም እያቃባህ ነው፤ የውጭ ወራሪን ሳይሆን ፍትህ የናፈቀውን የገዛ ራስህን ወገን እንድትወጋ እያደረጉህ ነው፤ አገርህ ለጥቂቶች ብቻ የምትታለብ ጥገት ሆና ለማቆየት አንተን በመሣሪያነት እየተጠቀሙብህ ነው። የነፃነት ኃይሎች ትግል የገጠሙት ከህወሓት ዘራፊ ወታደራዊና ሲቪል መሪዎች ጋር እንጂ ከአንተ ጋር አይደለም። እነሱ ሁኔታው አላምር ሲል መሸሻ አዘጋጅተዋል፤ እድሜ ልካቸውን በልተው የማይጨርሱት ሀብት በውጭ አገራት አከማችተዋል። ያ ቀን ከመምጣቱ በፊት ግን አንተ የገዛ ወገንህን ገድለህ እንድትጨርስ፤ አሊያም በገዛ ወገንህ ተገድለህ እንድትጠፋ ይሻሉ። እንደምታውቀው በገባንበት ትግል አንተ ብቻ ተኳሽ፤ አንተ ብቻ ገዳይ አይደለህም። የነፃነት ኃይሎች ሊገላቸው የመጣን ኃይል ከመግደል አይመለሱም። በአሁን ሰዓት እንኳን ቁጥራቸው ቀላል የማይባል የሠራዊቱ አባላት በነፃነት ኃይሎች ተጋድሎ መውደቃቸውን ታውቃለህ። ይህ መሆኑ ያሳዝነናል፤ ልትገድለን ስትመጣ ግን ባዶ እጃችንን አንጠብቅህም። እርስ በርስ የሚያጋድለን የህወሓት አገዛዝ ማብቃት አለበት። አንተ የዚህን እኩይ ስርዓት ትዕዛዝ አልቀበልም፤ ከድንበር መጠበቅ ውጭ የሀገሬን ህዝብ አልገልም ያልክ ቀን፤ ይህ ጦርነት ይቆማል። እንደልባቸው የሚያዙት ጦር እንደሌለ ሲያውቁ የሀገሪቱን የፖለቲካ ችግር በጉልበት ሳይሆን በፖለቲካዊ መንገድ ለመፍታት ይገደዳሉ። ለነጻነትና ለእኩልነት እየተዋደቁ ያሉት ወገኖችህ ልክ እንዳንተ ይህ በአንድ ሀገር ህዝቦች መሀከል የሚደረግ ጦርነት እንዲቆም ይፈልጋሉ። በረሀ የገቡት ገበሬ ዘመዶችህ በሰላም አርሰው ልጆቻቸውን አሳድገው ጥሩ ዜጋ ማድረግ ይፈልጋሉ። መገደል፤ መታሰርና መሰቃየት ሰልችቶት በረሃ የገባው ወጣት ሀገሩ ሰላም ሆና፤ የነጻነት አየር እየተነፈሰ ትምህርቱን በነጻ አዕምሮ ተምሮ ለሀገሩ በጉልበቱና በእውቀቱ አስተዋጽኦ ማድረግ የሚፈልግ እንጂ የጦርነት አባዜ ኖሮበት አይደለም በረሃ የወረደው። ስለዚህ ይህን ጦርነት ማስቆም የምትችለው አንተ ነህ። ይህን የምታደርገው ደግሞ እንዳንተ ሰላምና ነጻነት የሚፈልገውን ወገንህን በመግደል ሳይሆን አንተንም መላው ህዝቡንም አዋርደው መግዛት የሚፈልጉትን ጥቂት ዘራፊዎች እምቢ ማለት ስትችል ነው።

ከዛሬ ጀምሮ የተገኘውን ሁሉ አጋጣሚ ተጠቅመህ ሥርዓቱን በመክዳት የነፃነት ኃይሎችን ተቀላቀል። የሕዝብ ወገኖችን እንድትወጋ ስትታዘዝ እንድትወጋቸው ከተላክባቸው የነጻነትና የእኩልነት ታጋዮች ጋር ተቀላቀል። በአገኘኅው አጋጣሚ ሁሉ በግልም በቡድን መሣሪያህን ወደጥጋበኛ ህወሓት አዛዦችህ አዙር።

በሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች ከነፃነት ኃይሎች ጋር የሚቀላቀሉ የሠራዊቱ አባላት የክብር አቀባበል ይደረጋል። ሠራዊቱን የሚቀበሉ የሚያስተናግዱ፣ የሚያቋቁሙ ቡድኖችን በየቦታው አደራጅተናል። ሕዝብ በህወሓት አገዛዝ ላይ እንጂ በአንተ በሠራዊቱ አባል ላይ የያዘው ቂም የለም። እንዲያውም አንተ ራስህ ትግሉን እንድትቀላቀል ይፈልጋል። በሕዝብና በአገር ላይ በደል ሲፈጽም የኖረው የህወሓት አገዛዝ ፍፃሜለማፍጠን በሚደረገው ትግል የአንተ አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው።

በኢትዮጵያችን ውስጥ እንዲኖር የምንፈልገው ሠራዊት ታማኝነቱ ለፓርቲ ሳይሆን ለሀገር የሆነ፤ ድንበሯን ከጠላት የሚከላከል፤ በሀገር ፍቅር ስሜት የነደደ፤ ሕዝብ የሚወደውና የሚያከብረው ሠራዊት ነው። ይህ ሠራዊት የሚገነባው በአንተው ነው። የህወሓት ወንበዴዎች ከዚህ በፊት እንዳደረጉት ሠራዊቱን የመበተን ዓላማም ሆነ ፍላጎት ያላቸው የነፃነት ኃይሎች የሉም። እነኝህ ብልሹ መሪዎቹ ተወግደውለት መዋቅሩ እንደተጠበቀ፤ ሹመትና የደሞዝ ጭማሪ በችሎታና ባደረገው አስተዋጽኦ ብቻ እንጂ ለአንድ ድርጅት ባለው ድጋፍ ወይም በዘውግ ማንነቱ ያልሆነ፤ ሙያውና ተጋድሎው ሀገሩን ከጠላት መጠበቅና የህዝቡን ደህንነት ማረጋገጥ የሆነ፤ በተልዕኮ ላይ ቢሰዋ ህዝቡ እንደጀግና የሚቀብረው፤ አካለ ስንኩል ቢሆን ህዝቡ በአክብሮት እስከ እድሜ ልኩ የሚጦረው፤ መለዮ ለብሶ በህዝቡ ውስጥ ሲገኝ ወጣቱ እንደሱ ለመሆን የሚመኘው አኩሪ የኢትዮጵያ ሠራዊት ሆኖ እንዲቀጥል ነው ፍላጎታችን። ይህ ምኞት እንዲሳካ ግን ዛሬ የምትፈጽፈው ተግባር ወሳኝ ነው።

ውድ የአገሬ መለዮ ለባሾች፤

ለዴሞክራሲ ሲሉ እየታገሉ በሞቱትና አሁንም በሚታገሉት የሕዝብ ኃይሎች ስም የማቀርብላችሁን ጥሪ አድምጡኝ። ነፃ ሊያወጣችሁ እየታገለ ባለ ሕዝብ ላይ ፈጽሞ አትተኩሱ። ሕዝብ ላይ መተኮስ ማለት፤ የነፃነት ታጋዮች ላይ መተኮስ ማለት፤ በገዛ ራሳችሁ ላይ መተኮስ ማለት እንደሆነ እወቁ። ጤነኛ አዕምሮ ያለው ሰው እንዴት በገዛ ራሱ ጭንቅላት ላይ ይተኩሳል? የእስከዛሬው በቅቶን ከእንግዲህ መንገዳችሁን አስተካክሉ። ከቻላችሁ ይህን የባርነት አዋጅ ለማስፈጸም ስንል ከሕዝብ ጋር አንዋጋም ብላችሁ በኅብረት ቆማችሁ ይህንን ጦርነት አስቁማችሁ ሀገሪቱን ወደ ሰላማዊ የፖለቲካ ሽግግር ለመውሰድ ታገሉ። ይህን ካልቻላችሁ የሕዝብን ትግል ተቀላቀሉ። በግልም ይሁን በቡድን መሠሪ የህወሓት ጄኔራሎችና አለቆቻችሁን በማስወገድ የጀግንነት ታሪክ ሥሩ።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትና ፓሊስ አባላት ሆይ!

የኛ ፍላጎት ፍትህ፣ ነፃነት፣ እኩልነትና ዲሞክራሲ የሰፈነባት ኢትዮጵያ እዉን ሆና ማየት ነዉ። የእናንተም ፍላጎት ከዚህ የተለየ አይደለም። ከሕዝብ ጎን ቁሙ፤ ሕዝብ በጎናችሁ ይቆማል።

ኢትዮጵያ አገራችን በክብር ለዘላለም ትኑር!

Monday 18 September 2017

በወቅቱ የአገራችን ሁኔታ ላይ የአርበኞች ግንቦት 7 መግለጫ

መስከረም 6 2010
አገራችን ኢትዮጵያ የምትገኝበት ወቅታዊ ሁኔታ እጅግ በጣም አሳሳቢ ነው። ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) በኢትዮጵያዊያን ላይ በተለያዩ ግንባሮች ጦርነት ከፍቷል።
በሰሜን ጎንደር ጭልጋ፣ መተማና ሽንፋ አካባቢዎች ከፍተኛ ቁጥር ያለው ወታደር ሰፍሮ ሕዝብን ለመፍጀት ትዕዛዝ እየተጠባበቀ ነው። የአማራና የቅማንት ተወላጆችን ለማጋጨት ሲሸረብ የነበረው ዱለታ የመጨረሻ ደረሻ ላይ ደርሷል። የህወሓት አገልጋይ መሆኑ በተደጋጋሚ ባረጋገጠው የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚነት ይካሄዳል የሚባለው ሕዝበ ውሳኔ ግጭትን ከማስፋት በስተቀር የሚኖረው ጠቀሜታ የለም። ሕዝበ ውሳኔው በራሱ አስፈላጊ አልነበረም፤ ይደርግ ከተባለም ምርጫው ሊያስፈጽም የሚችል ተዓማኒን ተቋም የለም። የሕዝበ ውሳኔው ውጤት ከምዝገባው በፊት መገመት የሚቻል ቢሆንም ድምፆች ተገልብጠው የውሸት ውጤቶች ይፋ እንደሚሆኑ ከወዲሁ መናገር ይቻላል። ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ከተቋቋመ ጀምሮ አንዴም ተዓማኒነት ያለው ምርጫ አስፈጽሞ የማያውቅ በመሆኑ አሁን የተለየ ነገር ይፈጽማል ብሎ ተስፋ ማድረግ አይቻልም። የአማራ ክልልና የትግራይ ክልል ተፈራረሙ የሚባለው የድንበር ማካለል ጉዳይም ሌላው ተቀጣጣይ እሳት ነው። ይህ ስምምነት የብአዴን አመራሮች የህወሓት አገልጋይነታቸውን መሬት በይፋ በመስጠት ያረጋገጡበት ሰነድ ሆኖ በሕዝብ ልብ ተመዝግቧል። ለወልቃይትና ቅማንት ጥያቄዎች ፈጽሞ የተለያዩ ምላሾችን መስጠት በራሱ ጠብ ጫሪነት ነው። ከዚህም በተጨማሪ ሰሜን ጎንደርን በሶስት ዞኖች የመሸንሸን እቅድ አለ። ህወሓት አማራን በአጠቃላይ፤ በተለይ ደግሞ ጎንደርን ለማዳከም ዘርፈ ብዙ ፕሮጀክቶችን ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ነው።
በሶማሊ ክልል ያለው ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ነው። በጅጅጋ ከተማ እየተፈፀመ ያለው የዘር ምንጠራ የህወሓት አገዛዝ አገራችንን ወደየት እየወሰዳት እንደሆነ አመላካች ነው። የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ ወገኖቻችን ከየቤታቸው እየታደኑ ከክልሉ እንዲወጡ ተደርገዋል፤ ተደብደበዋል፣ ተደፍረዋል፤ ንብረታቸው ተዘርፏል። ይህንን ዘርን የማጥራት ሥራ በበላይነት የሚመራው የሶማሊ ክልል ልዩ ጦር መሆኑ ሁኔታው ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል። “የሶማሊ ልዩ ጦር ምንድነው? የማነው? ለምንድነው የተቋቋመው?” የሚሉ ጥያቄዎች አፋጣኝ ምላሽ ይሻሉ። ወገኖቻችን ለሰቆቃ የሚዳረጉት በመታወቂያቸው ላይ የተፃፈው ብሄር እየታየ መሆኑ ለሶማሊ ብቻ ሳይሆን ለሌላውን የኢትዮጵያ ክፍል አስደንጋጭ የማስጠንቀቂያ ደወል ነው። በሶማሊና በኦሮሚያ አዋሳኝ መንደሮችና ከተሞች እየተደረገ ባለው ከመደበኛ ጦርነት ያልተናነሰ ግጭት ሳቢያ የወገኖቻችን ሕይወት እየተቀሰፈ ነው፤ ይህን የሚፈጽመው ደግሞ የአገዛዙ አካል የሆነ ዘመናዊና ትጥቅና ስልጠና ያለው የጦር ሠራዊት ነው።
የሐረሪ ክልላዊ መንግሥት አለ ለማለት በሚያስደፍር ሁኔታ ላይ አይደለም። ሆኖም፣ አርበኞች ግንቦት 7ን የሚያሳስበው ችግር የሐረር ከተማና ዙርያው ነዋሪ ሕዝብ ሰላምና ደህነት እንጂ የክልላዊው መንግሥት መኖር አለመኖር አይደለም፤ የክልሉ አስተዳደር ከመነሻው ጀምሮ ችግር ያለበት ነው። አሁን ያለው ሁኔታ ግን ከዚህ በፊት ከነበረው ይለያል። ሐረር ከተማና ነዋሪዎቿ አደጋ ላይ ናቸው።
በግልብ ሲታይ ቅራኔው በአንድ በኩል ህወሓት፣ ሶህዴፓና ሐብሊ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ብአዴንና ኦህዴድ የተሰለፉ ይመስላሉ። ይህ ግን የተሳሳተ ምስል ነው። ብአዴንና ኦህዴድ ራሳቸው የህወሓት ስሬቶች ናቸው። የኢትዮጵያ ሕዝብ በህወሓት አገዛዝ ምን ያህል የተማረረ መሆኑ እና ለውጥ የሚፈልግ መሆኑ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተከታታይ በታዩ የተቃውሞ እንቅስቃሰዎች ገልጿል። የሙስሊም ወገኖቻችን ድምፃችን ይሰማ፤ የኦሮሚያ፣ የአማራና የኮንሶ የሕዝባዊ እምቢተኝነት እንቅስቃሴዎች እና በቅርቡ መላው አገሪቱን ያዳረሰው የግብር ማዕቀብ የኢትዮጵያ ሕዝብ በህወሓት አገዛዝ ምንያህል የተሰላቸ መሆኑን ገላጮች ናቸው። ህወሓት ከዚህ ቀውስ ለመውጣት የሕዝብን ጥያቄዎች ከመመለስ ይልቅ ሌሎች ቀውሶችን መፍጠር መርጧል። አሁን እያየነው ያለነው መተራመስ የዚህ እኩይ ውሳኔ ውጤት ነው። ህወሓት ራሱን ከአጣብቂኝ ለማውጣት መፍትሄ አድርጎ የወሰደው ሕዝብን ከሕዝብ አጋጭቶ ተጠያቂነትን ወደ ብአዴንና ኦህዴድ ማዞር ነው። በዚህም ምክንያት ህወሓት የጥፋት በትሩን የራሱ ስሪት በሆኑት ብአዴንና ኦህዴድ ላይ ሰንዝሯል፤ በሚቀጥሉት ሳምንታትና ወራት ውስጥ በእነዚህ ድርጅቶች መሪዎች ላይ የሚደርስ ህወሓታዊ ጥቃት እንደሚኖር መጠበቅ ብልህነት ነው።
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አገራችን ያለችበት አሳሳቢ ሁኔታ ይገነዘባል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ ከህወሓት በሚወረወሩለት የማዘናጊያ አጀንዳዎች ከትግሉ ሳይናጠብ ሙሉ ትኩረቱን አገዛዙን የመቀየር ትግል ላይ እንዲያደርግ ያሳስባል።
በየቦታው እየፈነዳዱ ያሉ ችግሮች ሁሉ ምንጫቸው ህወሓት ነው። የችግሮቹ መፍትሄ ያለውን ህወሓትን ማስወገድና በምትኩ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይሁንታ ያገኘ መንግሥት ማቆም ነው። ይህን ለመፈፀም በዲሞክራሲያዊ ኃይሎች መካከል ሰፊ የሆነ ትብብር መፍጠር ያስፈልጋል። አርበኞች ግንቦት 7 ከኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር፣ ከአፋር ሕዝብ ፓርቲና የሲዳማ ሕዝብ ዲሞክራሲያን ንቅናቄ በጋራ ለመሥራት የኢትዮጵያ አገራዊ ንቅናቄ (ኢአን) መፍጠሩ ይታወቃል፤ ከኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር ጋርም የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። በእንዲህ ዓይነት ወቅት እነዚህ ስምነነቶች አገራችን ለማዳን ወሳኝ ናቸው። ሌሎች ድርጅቶችም እንዲቀላቀሉን ጥሪዓችንን እናቀርባለን።
የህወሓትን የስልጣን ዘመን እያበቃ ነው። አርበኞች ግንቦት 7 የሕዝብን ፀረ ህወሓት ሁለገብ ትግል እያስተባበረ ይገኛል። አርበኞች ግንቦት 7 በመላው ኢትዮጵያ በሕዝብ ጋር ሆኖ የህወሓት አገዛዝን እየተፋለመ መሆኑን ይገልፃል። ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ቆመን የምናደርገው ትግል ለፍሬ እንደሚበቃ ጥርጥር የለውም።
ብአዴንና ኦህዴድ ውስጥ ያሉ ልባም ወገኖች ዛሬ ከሕዝብ ትግል ጎን ቢቆሙ ራሳቸውን ከማዳን ባለፈ ለአገርና ለወገን መልካም እንደሠሩ ሊቆጠርላቸው እንደሚችል አለበለዚያ ግን ከአገዛዙ ጋር መጥፋታቸው የማይቀር መሆኑን እንዲገነዘቡ አርበኞች ግንቦት 7 ያሳስባል። ስለሆነም ከህወሓት ጋር አብራችሁ ለራሳችሁም ለወገኖቻችሁም መከራና ሰቆቃ አትሸምቱ።
የወቅቱ የአገራችን ችግሮች የሚወገዱት ትግላችንን አቀናጅተን ህወሓትን ስናስወግድ ብቻ ነው። ይህንን ትግል በግባር ቀደምትነት ለመምራት አርበኞች ግንቦት 7 በፊት መስመር ተሰልፏል። በአንድነት ድል እናደርጋለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!
አንድነት ኃይል ነው!

The Intercept የሚባለው ሚስጥር አውጪ ህውሃት በበላይነት የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስትን ሚስጥር ማስፈትለኩን ታወቀ

የአሜሪካንና የሌሎች መንግስታትን ድብቅና ከፍተኛ ሚስጥር በማጋለጥ የሚታወቀው ዘ ኢንተርሴፕት (The Intercept)የሚባለው ሚስጥር አውጪ (Whistle blower) በመስከረም 13 ቀን 2017 እኤአ ህውሃት በበላይነት የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስትን ሚስጥር ማስፈትለኩን ታወቀ።

ይህን በሃይለማርያም ደሳለኝ ቁንጮነት የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት ጥብቅ ሚስጥርን ይዞ ወደ አደባባይ የወጣው በአሜሪካ መንግስት ተፈላጊ ከሆኑ ግለሰቦች መካከል በቀዳሚነት የተሰለፈው የቀድሞው የስለላ አባል የሆነው ኤድዋርድ ስኖውደን (Edward Snowden)እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል።
ኤድዋርድ ስኖውደን በአሜሪካ መንግስት በከፍተኛ ሚስጥርነት የተያዙትን መረጃዎች ለዊክሊክስ በማስተላለፉ ምክንያት በሩሲያ የጥገኝነት ህይወት እየመራ እንደሚገኝ ይታወቃል።
የአሜሪካ መንግስት በስልጣን ላይ ካለው የህውሃት አገዛዝ ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ምድር እያደረገ ያለውን ከፍተኛ የስለላ ሚስጥር መረጃ ዘ ኢንተርሴፕት (The Intercept) በተባለው የሚስጥር አውጪ ሊጋለጥ መቻሉን ለመረዳት ተችሏል።
ዘ ኢንተርሴፕት (The Intercept) ይህን ጥብቅ መረጃ ያገኘው ከኤድዋርድ ስኖውደን የሚስጥር ፋይል እንደሆነም ገልጿል።
በመንግስታቶች የሚከናወኑ ከፍተኛ ሚስጥሮችን (classified information) በማጋለጥ የሚታወቀው ዘ ኢንተርሴፕት(The Intercept) በመስከረም 13 ቀን 2017እኤአ ለህትመት ባወጣው ዶክመንት የአሜሪካው የስለላ አካል የሆነው NSA (National Security Agency) ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በመተባበር በምስራቅ አፍሪቃ ግዙፍ የስለላ ተቋም መገንባቱ በማስረጃ ለአለም አሳውቋል።
ይህ ዘመናዊ መሆኑ የተነገረለት የስለላ ተቋም ኢትዮጵያኖችን ጨምሮ በምስራቅ አፍሪቃ የሚገኙ አጎራባች አገራት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴዎች እንዲሁም የሚያደርጉትን የስልክና የኢንተርኔት ንግግሮች ወይም ግንኙነቶች በመጥለፍ የስለላ ተግባሩን እንደሚያከናውን ዘ ኢንተርሴፕት(The Intercept) አጋልጧል።
NSA (National Security Agency) በመባል የሚታወቀው የአሜሪካ የስለላ ተቋም የኢትዮጵያ መንግስት ላበረከተለት የቦታ እና የሰው ሃይል ስጦታ ውለታን በውለታ ለመመለስ የአምባገነኑን የኢትዮጵያ ሃይሎችን በኤሌትሮኒክ ሰለላ (electronic surveillance) ስለጠና መስጠቱ በዶክመንቱ ተጋልጧል::
የኢትዮጵያ መንግስት የኤሌክትሮንክስ የስለላን ዘዴ የተጠቀመበት ሽብርተኝነትን ወይንም ደግሞ ወንጀልን ለመዋጋት ሳይሆን የገዛ ዜጋውን ወይም ህዝቡን ለማሰቃየት እንደሆነ ዘ ኢንተርሴፕት (The Intercept) ከፍተኛ የሆኑ የሰብአዊ መብት ተመራማሪ የሆኑትን Mr. Felix ጠቅሶ ዘግቧል።
የአሜሪካው National Security Agency በየካቲት 2002እኤአ በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያውን የአንበሳ ኩራት (Lion’s Pride) ተብሎ የሚጠራውን የስለላ ማዕከል ማቋቋሙን ይህ ዶክመንት ይጠቁማል።
ይህ የስለላ ማዕከል እንደተቋቋመ ቀለል ያለ ሚሽን (ተልእኮ) የሚመሩ አስራ ሁለት ኢትዮጵያውያኖች ብቻ እንደነበሩትም ተዘግቧል።
ነገር ግን በ2005እኤአ ይህ ቁጥር በሚያስገርም ሁኔታ አድጎ ስምንት የአሜሪካ ወታደራዊ ፕርሶኔል እና መቶ ሶስት ኢትዮጵያዊያኖች ተሰማርተው እንደሚገኙ ለመረዳት ተችሏል።
ከዚህም በተጨማሪ ማዕከሉ ወደ አርባ ስድስት የሚሆኑ የስራ ቦታዎች እንደነበሩት ይሄው ዶክመንት አያይዞ ገልጧል።
ዘ ኢንተርሴፕት ያወጣው ሚስጥራዊው ዶክመንት እንደሚጠቁመው የአሜሪካው የስለላ አካል የሆነው NSA አዲስ አበባ ከሚገኘው የስለላ ማእከሉ በተጨማሪ በድሬዳዋም በ2006እኤአ ሁለተኛውን የሰለላ ተቋም መዘረጋቱን ለማወቅ ተችሏል።
በድሬዳዋ የተቋቋመው የስለላ ማዕከል በህዝቦች መካከል የሚደረገውን ግንኙነት በተለይ ደግሞ በሶማልያ፣ ሱዳን እና በምስራቅ ኢትዮጵያ የሚደረጉ ማንኛውንም የኤሌክትሮኒክ ግንኙነትን ወይም ንግግርን የሚያዳምጥ መሆኑን ይሄው ዶክመንት አስፍሯል።
በሌላ በኩል ደግሞ የአሜሪካ መንግስት እና የኢትዮጵያ መንግስት በመተባብር በኡጋዴንና በሶማሊያ ጠረፍ እካባቢ የሚደረገውን የህዝቦች ግንኙነት የድሬዳዋውን ማዕከል በመጠቀም መሰለላቸውን ሚስጥራዊው ማስረጃ ያትታል።
የጥቁር ኩራት ወይም Lion’s pride ተብሎ የሚጠራው የስለላ ማዕከል በአዲስ አበባ እና በድሬዳዋ ከተመሰረቱት ማዕከላት በተጨማሪ በጎንደር አካባቢም ሶስተኛ ማዕከል መከፈቱን የኢንተርሴፕት Intercept የምርምር ዶክሜንት ጨምሮ ገልጧል።
የአሜሪካ የስለላ ድርጅት በዑጋዴን አካባቢ የሚደረገውን እንቅስቃሴ በመሰለል የኢትዮጵያ መንግስት በንጹሃን ዜጎች ላይ ለፈጸመው አሰቃቂ ግድያ ተባባሪ መሆኑ እጅግ በጣም አስነዋሪ ነው በማለት የሰብአዊ መብት ተመራማሪ የሆኑት Mr. Horne ቅሬታቸውን ገልጸዋል።
ዘ ኢንተርሴፕት the Intercept ባወጣው በዚህ ዶክመንት በአሁኑ ሰአት እነዚህ ከአሁን በፊት በአዲስ አበባ ፣ በድሬዳዋ እንዲሁም በጎንደር የተከፈቱት የስለላ ማእከላት መዘጋታቸውን የሚያሳይ ምንም ማስረጃ እንዳላገኘ ዘግቧል።
አያይዞም የአሜሪካ መንግስት ከዚህ አሳፋሪ እና ህገወጥ ድርጊቱ መቆጠብ ይኖርበታል ሲል አሳስቧል።

Friday 7 July 2017

ኢህአዴግ በሙሉ ሃይሉ ተጠቅሞ የድጋፍ ሰልፎች እንዲደረጉና ፖለቲካዊ ኪሳራውን እንዲሸፈን ጥብቅ ትእዛዝ ሰጥቷል

የግንባሩ የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት የኦሮሞ ህዝብ በአዲስ አበባ ላይ ያለውን ልዩ ጥቅም የሚያስከበር አዋጅ መደንገጉ ለድርጅቱ ከፍተኛ ህዝባዊ ድጋፍ ያስገኝለታል በሚል በኢህአዴግ የፖሊሲ፣ ጥናትና ምርምር ተቋም የቀረበው ምክር እንዳልሰራ በመታመኑ ፣ ሰነዱ በኦሮምያ ክልል በየደረጃው ባሉ አካላት ውይይት ተካሂዶበት፣ የድጋፍ ሰልፍ እንዲደረግለት ልዩ ትዕዛዝ ተላልፏል። በአቶ በረከትና አባይ ጸሃዬ የሚመራው የምርምር ተቋም፣ የአዲስ አበባን ስም መቀየር እንዲሁም የተጠቃሚነት መብታቸውን ማወጁ ዳር እስከዳር በሰልፍና በፈረስ ድምቀት የፈጥራል የሚል ምክር ለግሶ ነበር። ከአዋጁ በሁዋላ የተደረገው ግምገማ ግን አዋጁ በተቃራኒው በተቀናቃኝ የኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ ዝምድናን በማንገሱ እንዲሁ ሌሎች ተጨማሪ ጥያቄዎችን በማስነሳቱ፣ ኢህአዴግ በሙሉ ሃይሉ ተጠቅሞ የድጋፍ ሰልፎች እንዲደረጉና ፖለቲካዊ ኪሳራውን እንዲሸፈን ጥብቅ ትእዛዝ ሰጥቷል። ብአዴን በበኩሉ “ከኦሮሞ ህዝብ ድጋፍ መታጣቱን የተመለከቱ የህወሃት የማህበራዊ ምንደኞች፣ አማራን በማነሳሳት አማራና ኦሮሞን ለማጋጨት የሚያደረጉትን ጥረት ኢህአዴግ ያስታግስልኝ” ሲል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የህወሃት ደጋፊ የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች በአማራ ክልል ፕሬዚዳንትና ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ ላይ የጀመሩትን የስድብ ዘመቻ አንስቶ ለኢህአዴግ አቅርቧል። በስብሰባው ላይ በህወሃትና በብአዴን መካከል ያለው ክፍተት እየሰፋ መሄዱን ምንጮች ገልጸዋል። ብአዴን በክልሉ ፕሬዚዳንት ላይ በማህበራዊ ሚዲያ የተከተፈተውን ዘመቻ ህወሃት የሚመራ ነው ብሎ ያምናል። ህወሃት በበኩሉ ግለሰቦች የራሳቸውን ሃሳብ የመሰንዘር መብት እንዳላቸው በመግልጽ፣ ሃላፊነቱን ከራሱ ለማሸሽ ይሞክራል። ብአዴን፣ በኦሮምያና አማራ አካባቢዎች የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ ህወሃት እየተዳከመ የመጣውን የመሪነት ቦታውን መልሶ ለመያዝ፣ በማህበራዊ ሚዲያ ባሰማራቸው አባሎቹ አማካኝነት አንዱ ህዝብ የሌላው ጠላት እንደሆነ አድርጎ እያቀረበ የኦህዴድን ድጋፍ በመያዝ ብአዴንን ለማዳከም እየሞከረ ነው በማለት ወቀሳ ሲያቀርብ፣ ህወሃት በበኩሉ በአማራ ክልል ጸረ ህወሃት አቋም እንዲጸባረቅና ህወሃት የከፈለውን መስዋትነት በመካድ ፣ ህወሃት በአማራ ህዝብ ዘንድ ተቀባይነት እንዳይኖረው የተወሰኑ የብአዴን አመራሮች ውስጥ ለውስጥ ስራዎችን እየሰሩ ነው ብሎ ያምናል። ለጊዜው አንዱ በሌላው ላይ አፋጣኝ እርምጃ በመውሰድ አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት አገሪቱ ያለችበት ሁኔታ ባይፈቅዱም፣ በብአዴን እና በህወሃት መካከል የሚታየው ልዩነት እየሰፋ እንጅ እየጠበበ እንደማይሄድ ምንጮች ይናገራሉ። ህወሃት ኦህዴድን በመያዝ የህወሃትን የበላይነት በሚቀናቀኑ የተወሰኑ የብአዴን መሪዎች ላይ እርምጃ ለመውሰድና ድርጅቱን መልሶ በስሩ ለማድረግ የሚጠቀምበት ስልት ሊሳካ መቻልና አለመቻሉ በኦህዴድ አቋም ይወሰናል የሚሉት እነዚሁ ምንጮች፣ ብአዴን የህሃት ካድሬዎች በአማራና ኦሮሞ መካከል ችግር ለመፍጠር እየሰሩና ይቁምልኝ ከማለት ውጭ፣ ከኦህዴድ ጋር የተለዬ ግንኙነት ሲመሰረት አይታይም ይላሉ። የኦሮሞ ህዝብ አዲስ የወጣውን የአዲስ አበባ አዋጅ ውድቅ ማድረጉ በብአዴኖች ዘንድ ውስጥ ለውስጥ ደስታን ሳይፈጥር እንዳልቀረም ምንጮቻችን ይገልጻሉ። አዋጁ በህዝቡ ዘንድ ተቀባይነት ቢያገኝ ኖሮ ህወሃት ቅደመ ሁኔታ የሌለበት ድጋፍ ( unconditional support) ከኦህዴድ በማግኘት ተጠናክሮ እንዲወጣና በብአዴን ላይ የፈለገውን እርምጃ ለመውሰድ እንዲያስችለው ያደርግ ነበር በማለት የብአዴን መሪዎችን በቅርብ የሚያውቁት ምንጮች ትንታኔያቸውን ያቀርባሉ። ሰሞኑን በባህርዳር ለ3 ቀናት የተካሄደው የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣኖች ስብሰባ በዋነኝነት በሁለቱ ድርጅቶች መካከል ያለውን አለመተማመንና ጥርጣሬ ለማስወገድ ያለመ ነበር።
ኢሳት ዜና

Wednesday 31 May 2017

የህወሃት መሪዎች የትግራይ ተወላጅ ያልሆነ ኢትዮጵያዊ በአለም አቀፍ ተቋማት ውስጥ በሃላፊነት እንዲሰራ ድጋፍ እንደማያደርጉ ተገለጸ

በኢትዮጵያ የፖለቲካ ስልጣኑን የያዙት የህዝባዊ ወያኔ ሃርነት መሪዎች የትግራይ ተወላጅ ያልሆነ ኢትዮጵያዊ በአለም አቀፍ ተቋማት ውስጥ በሃላፊነት እንዲሰራ ድጋፍ እንደማያደርጉ አንድ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ ገለጹ።
በአፍሪካ ልማት ባንክ እስከ ምክትል ፕሬዚደንትነት ለ15 አመታት ያገለገሉት አንጋፋው ኢትዮጵያዊ አቶ ተካልኝ ገዳሙ “Republican on the Throne” በተባለውና ከአመታት በፊት ለንባብ ባቀረቡት መጽሃፋቸው እንደገለጹት ለአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዚደንትነት ሳይወዳደሩ የቀሩት የኢትዮጵያ መንግስት የድጋፍ ወረቀት ስለነፈጋቸው መሆኑን አውስተዋል።
ይህ በእርሳቸው እንዳልተጀመረና ከርሳቸው በፊትም በሌሎች የትግራይ ተወላጆች ባልሆኑ ኢትዮጵያውያን ላይ ተፈጻሚ መሆኑንም በመጽሃፋቸው ያመለከቱ ሲሆን፣ ለኢሳት በሰጡት ቃለምልልስ ይህንኑ በዝርዝር ተመልክተዋል።
የዩኒቨርስቲ ትምህርታቸውን በአሜሪካ ኤሊኖይና በስመጥሩ ሃርቫርድ ዩኒቨርስቲ ካጠናቀቁ በኋላ፣ በኒውዮርክ የተባበሩት መንግስታት ሰራተኛ በመሆን ስራ የጀመሩት አንጋፋው ኢትዮጵያዊ አቶ ተካልኝ ገዳሙ፣ ከቀዳማዊ ሃ/ስላሴ ዘመን በመጨረሻና በደርግ ዘመን በሚኒስትርነት ሃገራቸውን አገልግለዋል።
በፈቃዳቸው ስልጣናቸውን በመልቀቅ ወደ አቢጃን ኮትዲቪዋር በማምራት በአፍሪካ ልማት ባንክ እስከምክትል ፕሬዚደንትነት 15 አመታት ያልገለገሉት አቶ ተካልኝ ገዳሙ፣ በቦታው ባሳዩት ውጤታማነት ለፕሬዚደንትነት እንዲወዳደሩ ከተለያዩ ሃገራት አምባሳደሮች ግፊት ቢደረግም፣ በኢትዮጵያ መንግስት ድጋፍ ባለማግኘታቸው ሳይሳካ መቅረቱን ለኢሳት በሰጡት ቃለምልልስ አስታውሰዋል።
አቶ ተካልኝ ገዳሙ በመጽሃፋቸው እንዳመለከቱት የትግራይ ተወላጆች ያልሆኑ ኢትዮጵያውያን በአለም አቀፍ መድረክ ስፍራ እንዳያገኙ ድጋፍ መንፈግ የተጀመረው በርሳቸው እንዳልሆነና ሌሎች አብነቶችን ጠቅሰዋል።
አቶ ተፈራ ራስወርቅ የተባበሩት መንግስታት አካል ለሆነው ኢንተርናሽናል ቴሌኮሚኒኬንሽን ዩኒየን እንዳይወዳደሩ በመንግስት ድጋፍ መነፈጋቸውን አስታውሰው፣ አቶ ይልማ ታደሰም ለአፍሪካ ህብረት ያደርጉት የነበረውን ውድድርም በተመሳሳይ በመንግስት ለዜጎቹ በነፈገው ድጋፍ መስተጓጎሉም አመልክተዋል።
ስልጣን ላይ ያለው የኢትዮጵያ መንግስት የትግራይ ተወላጅና የህወሃት አባል የሆኑት ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ለአለም አቀፍ የጤና ድርጅት እንዲወዳደሩ ድጋፍ ከመስጠት ባሻገር የቅስቀሳ ስራ እንዲሰሩ ከ60 በሚበልጡ ሃገራት እንዲንቀሳቀሱ ሁኔታዎችን አመቻተዋል።
ምርጫው በተካሄደበት ጀኔቫም የመንግስት ልዑካንን የላከ ሲሆን፣ ዶ/ር ቴዎድሮስ አሸንፈው ወደ ሃገር ቤት ሲመለሱም የጀግና አቀባበል አድርጎላቸዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ ለሚገኙ የትግራይ ተወላጅ ወጣቶች በተዘጋጀው መድረክ ላይም ተገኝተው ደማቅ መስተንግዶ ተደርጎላቸዋል። የትግራይ ወጣቶችም የአቶ መለስና የዶ/ር ቴዎድሮስን አርዓያ እንዲሚከተሉ ገልጸዋል።
ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የአለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ሆነው መመረጣቸውን በተመለከተም በኢትዮጵያ መንግስት በኩል የተባበሩት መንግስታት ዋና ጸሃፊነትን ስልጣን የያዙ ያህል እየተጋነነ ይገኛል።የዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ስልጣን ከተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሃፊነት ጋር በማነጻጸር እንዲመለከቱ ኢሳት ያነጋገራቸው በጄኔቭ የኢትዮጵያ አምባሳደር የነበሩት ዶ/ር ካሳ ከበደ ልዩነቱን በአንድ ከተማ ከንቲባና በከተማው ውስጥ በሚኖር አንድ ሃኪም ቤት ሃላፊ ጋር አነጻጽረውታል።

ምንጭ:ኢሳት 

Monday 22 May 2017

አርበኞች ግንቦት 7 ቴድሮስ አድሃኖምን የሚያጋልጥ መረጃ ለቀቀ

የዓለም ጤና ጥበቃ ዳይሬክተርነት በህዝባችን ላይ የተፈጸመውን ወንጀል መሸፈኛ ሊሆን አይችልም!

አርበኞች ግንቦት 7

ህዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሥልጣን ከተቆጣጠረበት ጊዜ ጀምሮ እንደ ድርጅትና እንደ መንግሥት በአገራችን ውስጥ እንዲተገበሩ በወጡ አፋኝ ፖሊሲዎችና በህዝባችን ላይ በተወሰዱ ፋሽስታዊ እርምጃዎች ሁሉ ወሳኝ ሚና ከነበራቸው ጥቂት የድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮች መካከል ቴዎድሮስ አድሃኖም አንዱ ነው።

ይህ ወንጀለኛ ግለሰብ የአምባገነኖች ስብስብ በሆነው የአፍሪካ ህብረት ሙሉ ድጋፍ አግኝቶ ለአለም ጤና ጥበቃ ዳይሬክተርነት እጩ ሆኖ ሲወጣ እንደ ትልቅ ገድል የተቆጠረለት የጤና ጥበቃ ሚንስቴር ሆኖ ባገለገለባቸው አመታት አስመዝግቧል የተባለው የጤና መሻሻልና በውጪ ጉዳይ ሚንስትርነት አበርክቷል የተባሉት አስተዋጾዎች ናቸው።
ምዕራባዊያን ለጋሾች ለታዳጊ አገራት የጤና አገልግሎት በየአመቱ የሚሰጡትን ገንዘብ የሚመድበውና የመደበውን ገንዘብ ሥራ ላይ መዋሉን የመከታተል ሃላፊነት የተጣለበት ግሎባል ፈንድ የተባለው አለም አቀፍ ተቋም ቴዎድሮስ አድሃኖም የአገራችንን ጤና ጥበቃ ሚንስትር መሥሪያ ቤት በመራበት ወቅት ለነፍስ አድን ዕርዳታ ከሰጠው አንድ ቢሊዮን ሶስት መቶ ስድስ ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ውስጥ ከፍተኛውን ገንዘብ እንዴት አድርጎ እንዳባከነና ለፖለቲካ ፍጆታ እንደዋለ በኦዲተሮቹ አስመርምሮ ይፋ አድርጓል።

ሜይ 14 ቀን 2012 ዓም ይፋ የሆነው ይህ የምርመራ ሪፖርት እንደሚያትተው በፈረንጆች አቆጣጠር 2009 እና 2010 ለአገራችን የተሰጠው የነፍስ አድን እርዳታ ገንዘብ ዋና አላማው በደማቸው ውስጥ የኤች አይቪ ቫይረስ የተገኘ ፤ በሳምባ ህመምና በወባ የተጠቁ ሰዎችን ህይወት ከሞት ለማትረፍ የታሰበና የገንዘብ ድልድሉም የሚከተለውን የሚመስል ነበር።

• ለሳምባና ወባ ህክምና 404 ሚሊዮን ዶላር
• ለኤች አይቪ 879 ሚሊዮን ዶላር
• የኤች አይቪ ተሸካሚዎች ኔት ዎርክ 9 ሚሊዮን ዶላር
• በኤች አይቪ በሽታ ወላጆቻቸውን ላጡ ህጻናት መርጃ 14 ሚሊዮን ዶላር በድምሩ አንድ ነጥብ ሶስት መቶ ስድስት ሚሊዮን ዶላር

ከዜጎች ህይወትና ደህንነት በላይ የፖለቲካ ሥልጣን ዕድሜው እጅግ የሚያሳስበው የህወሃቱ ቴዎድሮስ አድሃኖም ግን ለነፍሰ አድን ከተሰጠው ከዚህ መጠነ ሰፊ ገንዘብ ውስጥ 165,393,027 /አንድ መቶ ስልሳ አምስት ሚሊዮን ሶስተ መቶ ዘጠና ሶስት ሺ ሃያ ሰባት/ የአሜሪካን ዶላር የለተቋሙ እውቅናና ፈቃድ 1309 ጣቢያዎችን አስገንብቻለሁ በማለት ገንዘቡን እንዳባከነ የግሎባል ፈንድ ኦዲተሮች ባደረጉት ምርመራ ደርሰውበታል። ከዚህም በተጨማሪ 57, 851, 941 ዶላር የት እንደገባ ማረጋገጫ አልተገኘለትም ።

የት እንደገባ ማረጋገጫ አልተገኘለትም የተባለውን ሃምሳ ሰባት ሚሊዮን ስምንት መቶ ሃምሳ አንድ ሺ ዘጠኝ መቶ አርባ አንድ ዶላር ጉዳይ የሚያውቀው ቴዎድሮስ አድሃኖም ብቻ ሊሆን እንደሚችል ገምተን ወደ ጎን እንተወውና በእርዳታ ገንዘቡ ተገንብተዋል ስለተባሉት ጤና ጣቢያዎች ሪፖርቱ የሚያወራውን እንመልከት ። በግሎባል ፈንድ የኦዲት ሪፖርት መሠረት ቴዎድሮስ አድሃኖም 1309 ጤና ጣቢያዎችን በተቋሙ ገንዘብ ገንብተናል ብሏል።
ከነዚህ 1309 ጤና ጣቢያዎች ውስጥ የግሎባል ፈንድ ኦዲተሮች 77ቱን እንዲጎበኝ ተደርጎ፤

• 71%ቱ ለጤና ጣቢያ እጅግ አስፈላጊ ከሆኑ ነገሮች ውስጥ አንዱ የሆነውን የውሃ አገልግሎት በጭራሽ እንደሌለው፤
• 32%ቱ ሽንት ቤት የሚባል ነገር እንዳልተሠራለት፤
• 53%ቱ ገና ተሠርተው ከማለቃቸው የህንጻዎች ወለሎች በከፍተኛ ሁኔታ ተሰነጣጥቀው መገኘታቸውን፤
• 19%ቱ ደግሞ ጣራቸው ማፍሰስ መጀመራቸውን አረጋግጦአል።

የወያኔን ባለሥልጣናት የሞራልና የሙስና ዝቅጠት ደረጃ ግምት ውስጥ አስገብተን ይህንን የኦዲት ሪፖርት ማንበብ ከፈለግን እነዚህ ለጉብኝት ክፍት የሆኑት 77 ጣቢያዎች በተሻለ የጥራት ደረጃ ላይ ይገኛሉ ተብለው የተገመቱና በዚህም የተነሳ ቢጎበኙ ለጋሾች ተጨማሪ ዕርዳታ ሊሰጡን ይችላሉ አለያም ደግሞ በተሠራው ሥራ ያወድሱናል በሚል እምነት ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም። ለጉብኝት ክፍት ያልነበሩት ቀሪዎቹ 1232 ህንጻዎች በምን ሁኔታ ላይ ሊገኙ እንደሚችሉ ከዚህ በመነሳት ማወቅ ይቻላል። ጭራሽ የመሠረት ድንጋይ ሳይጣል ተሠርተዋል ተብለው ሪፖርቱ ውስጥ የተጠቃለሉ ሊኖሩ እንደሚችልም መጠርጠር አይከፋም ። የኛ ነው የሚሉትን የትግራይ ህዝብ ነፍስ ለመታደግ በዚያ በ1977ቱ የድርቅ ወቅት ከአለም ለጋሾች የተላከን የዕርዳታ እህል ሽጠው በምትኩ አሸዋ በጆንያ ሞልተው ሂሳብ ያወራረዱ ሽፍቶች የፈረንጅ እግር በማይደርስባቸው የአገሪቱ ክፍሎች የጤና ጣቢያ ህንጻዎችን አስገንብተናል ብለው ገንዘቡን ቢበሉት ምን ያስገርማል?

የግሎባል ፋንድ ኦዲት ሪፖርት ከላይ በተገለጸው ብቻ አላቆመም ። ድርጅቱ ለነፍስ አድን በሰጠው ገንዘብ ህክምና እርዳታ ይሰጥባቸዋል የተባሉና አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ 46 የህክምና አገልግሎት መስጫ ተቋማትን ጎብኝተው አብዛኛዎቹ የቧንቧ ውሃ አገልግሎት እንደሌላቸው፤ ለበሽታ ናሙና ምርመራ የሚጠቀሙባቸው ማይክሮስኮፖች የተበላሹና ያረጁ በመሆናቸው በተለይ የወባና የሳምባ በሽታን በትክክል ለመለየት የማያስችሉ መሆናቸውን ፤ በ46ቱም ተቋማት ውስጥ ካሉ ዶክተሮችና ነርሶች ስለወባ በሽታ ማኔጅመንት አንዳቸውም ሥልጠና አግኝተው እንደማያውቁ፤ ለህመምተኞች የሚሰጠው መድሃኒት መበላሸት ወይም አለመበላሸቱ በወቅቱ ቁጥጥር እንደማይደረግበት ወዘተ መታዘባቸውን አጋልጠዋል።

የኢትዮጵያዊያንን ህይወት ለማትረፍ ግሎባል ፈንድ የሰጠው ገንዘብ በዚህ መልኩ መባከኑንና በእርዳታ ስምምነቱ ውስጥ ላልተገለጸ አላማና ተግባር መዋሉን ካረጋገጠ ቦኋላ ተቋሙ እርምጃ ለመውሰድ የጀመረውን እንቅስቃሴ በወቅቱ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚንስትር የነበረው ሟቹ መለስ ዜናዊ ጣልቃ ገብቶ እንዳከላከለና ለግሎባል ፈንድ የገንዘብ ዕርዳታ ከሚለግሱ የአለም ዲታዎች አንዳንዶቹ የተለያየ ግፊት ፈጥረው ተድበስብሶ እንዲቀር እንዳደረጉት የሚያጋልጥ መረጃ በእጃችን አለ።

እንግዲህ ቴዎድሮስ አድሃኖም የጤና አገልግሎቶችን አስፋፍቶአል በማለት ለአለም ጤና ጥበቃ ዳይሬክተርነት እያደረገ ባለው ዘመቻ በመናፈስ ላይ ካለው የፈጠራ ህይወት ታሪክ በስተጀርባ ያለው እውነታ ይህ እንደሆነ በርካታ ኢትዮጵያዊያን እናውቃለን። በዚህ ዘረፋ ምክንያት ህክምና አጥተው ህይወታቸው የተቀጠፈ ዜጎች ቁጥርም ውሎ አድሮ ጊዜ የሚያጋልጠው ይሆናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን።

ከዚህ ወንጀል በተጨማሪ የውጪ ጉዳይ ሚንስትር ሆኖ ባገለገለባቸው ጊዜያትም፡ ድርጅቱ ህወሃት በህዝባችን ላይ የፈጸማቸውን የጎዳና ላይ ጭፍጨፋዎች ፤ በየእስር ቤቱ በተወረወሩ የፖለቲካ እስረኞች ላይ የደረሰውን ሰቆቃና ግርፋት ፤ እንዲሁም እትብታቸው ከተቀበረበት ቦታ በጉልበት እንዲፈናቀሉ ተደርገው ለጎዳና ተዳዳሪነት የተዳረጉ በሺዎች የሚቆጠር ዜጎች ስቃይና መከራ ተሸፍኖ እንዲቀር የቻለውን ሁሉ አስተዋጾ አድርጎአል። የንቅናቄያችን ዋና ጸሃፊ የሆነውን ጓዳችን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ከየመን አየር ማረፊያ አሳፍኖ በመውሰድ ተግባር ውስጥም እጁ እንዳለበት እናውቃለን። የአጋዚ ጦር በቅርቡ በኢሬቻ በአል ላይ፤ በጎንደር፤ በባህርዳር ፤ በጌዶ ወዘተ የፈጸመውን ፋሽስታዊ ጭፍጨፋ ጀማሪ ዲሞክራሲ ስለሆን ህግ አስከባሪዎች በእውቀት ማነስ የፈጸሙት ነው በማለት እያናናቀ በተለያዩ አለም አቀፍ መድረኮች ላይ ተዘባብቶብናል።

እንዲህ አይነት ወንጀለኛን የአፍሪካ አምባገነኖችና አንዳንድ ለሰው ልጆች ሰብዓዊ መብት ደንታ የሌላቸው የአገራቸውን ጥቅም ብቻ ለማስከበር ደፋ ቀና የሚሉ ምዕራባዊያን መንግሥታት አሞጋግሰው ለአለም ጤና ጥበቃ ዳይሬክተርነት ቦታ ቢያነግሱትም ባያነግሱትም ፍትህ እኩልነትና ነጻነት በምድራች ኢትዮጵያ እውን በሚሆንበት ቀን በግልና በቡድን ከፈጸመብን ወንጀል ተጠያቂነት ሊያድኑት እንደማይችሉ ንቅናቄያችን አርበኞች ግንቦት 7 ያምናል።
የተባበሩት መንግሥታት አካል የሆነው የአለም ጤና ጥበቃ ድርጅት በእስከዛሬ ታሪኩ በሙያቸውና በሥነምግባራቸው የላቁ ሰዎችን እንጂ እንደ ቴዎድሮስ አድሃኖም ያሉ በሙያቸው የቀጨጩ ፤ ለፖለቲካ ፓርቲያቸው የሥልጣን ዕድሜ መራዘም ሲሉ ንጹሃንን በጠራራ ጸሃይ በማስጨፍጨፍ በሰው ደም የተጨማለቁ ወንጀለኞችን አስተናግዶ አያውቅም። ለንግዳቸው እንጂ ለጥቁር ህዝቦች ህይወት ደንታ የሌላቸው አለም አቀፍ ቱጃሮች እንደ ቴዎድሮስ አድሃኖም አይነት በጥቅም የሚገዛ ታዛዥ ሎሌ በቦታው ለማስቀመጥ እያደረጉ ያሉትን ሩጫ በቅርበት የሚከታተለው አርበኞች ግንቦት 7 የአለም ጤና ጥበቃ ጽ/ቤት የወንጀለኞች መደበቂያ ዋሻ ሊሆን እንደማይችል ይገነዘቡት ዘንድ ያሳስባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ