Tuesday, 27 October 2015

የመን የሚሰደዱ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ቁጥር መጨመሩ

ጥቅምት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መነሻቸውን ከሶማሊያ የባሕር ዳርቻዎች በማድረግ በሕገወጥ መንገድ ሕይወታቸውን ለአደጋ አልጋልጠው በጦርነት ሰላሟ ወደራቃት የመን የሚሰደዱ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ቁጥር መጨመሩን ዓለምአቀፉ የስደተኞች ድርጅት በምህጻረ ቃል /UNHCR/ አስታውቋል። ባለፈው ዓመት ብቻ ከ70 ሺ በላይ አዲስ ስደተኞች የመን መግባታቸውን የገለጸው ድርጅቱ፣ ጥቂት የሶማሊያ ዜጎች ሲገኙበት አብዛኞቹ ስደተኞች ኢትዮጵያዊያን ናቸው። 88 ስደተኞች በባሕር ውስጥ ሰጥመው መሞታቸውንም ድርጅቱ አስታውቋል። የመንን ለመሸጋገሪያነት በመጠቀም ወደ ተለያዩ የአረብ አገራት ለስራ ፍለጋ የሚመጡት ስደተኞች የተለያዩ የመብት ጥሰቶች እንደሚፈጸሙባቸውና በየመን ባለው የጸጥታ ችግር ምክንያት የምግብ እና የጤና አቅርቦት የተሟላ ባለመሆኑ የረድኤት ድርጅቶች አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ እንዳሉም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ሁለት አሃዝ አድጋለች እየተባለ በየቀኑ ቢነገርም ፣ ወጣት ኢትዮጵያዊያን ሕይወታቸውን ለአደጋ አጋልጠው በአራቱም ማእዘናት መፍለሳቸውን አለማቆማቸው ሲታይ የአገሪቱ ምጣኔ ሃብታዊ ለውጥ ትሩፋቶች ለሕዝቡ እንደልደረሰ ያመላክታል ሲሉ የሙያው ጠበብት ይገልጻሉ።

ብአዴን ወጪውን የሚሸፍነው በዋነኝነት ከነጋዴዎችና ከነዋሪዎች ነው

ጥቅምት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የኢሳት ምንጮች እንደገለጹት ብአዴን ወጪውን የሚሸፍነው በዋነኝነት ከነጋዴዎችና ከነዋሪዎች ነው። በርካታ የክልሉ ነጋዴዎች ገንዘብ እንዲለግሱ የጥሪ ወረቀት ደርሶአቸዋል። ድርጅቱ ከህወሃትና ከኦህዴድ ባላነሰ መልኩ በአሉን እንደሚያደርግ እየገለጸ ሲሆን፣ አገሪቱ ከፍተኛ የረሃብ አደጋ አንዣቦባት ባለበት እንዲሁም የኑሮ ውድነቱ የህዝቡን ኑሮ ፈተና ውስጥ በጣለበት ሰአት ይህን ያክል ገንዘብ ህዝቡን አስገድዶ በማውጣት ለማክበር ማሰብ ኢ-ሞራላዊና ህዝብን መናቅ ነው ሲሉ መረጃውን የላኩ የብአዴን አባላት ተናግረዋል። ብአዴን እመራዋለሁ የሚለውን ህዝብ ማወረዱን የሚገልጹት አባላቱ፣ ህዝቡ በሰበብ አስባቡ መዋጮ እንዲያወጣ መደረጉ ለድህነት ከመዳረጉም በላይ እለታዊ ህይወቱን ለመምራት በማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል። ከህወሃት ጋር በሽርክና የተያዙት የብአዴን ኩባንያዎች ለአማራው ህዝብ የፈየዱለት ነገር እንደሌለ አባሎቹ አክለው ገልጸዋል። በተለይ ዋናዎቹ አመራሮች እንደፈለጉ የሚዘርፉት የጥረት ሃብት ፣ አንድም ቀን ሂሳቡ ተመርምሮ ለህዝብ ይፋ ሆኖ አያውቅም ይላሉ። የጥረት ሃብት የአማራ ህዝብ ሃብት ነው ይባላል እንጅ፣ ህዝቡ ስለሃብቱም የሚያውቀው እንደሌለ የሚገልጹት አባሎቹ፣ በዚህ ፈታኝ ወቅት ብአዴን በአሉን ከጥረት ሃብት በማውጣት በማክበር የነጋዴውንና የህዝቡን ስቃይ መቀነስ ይችል ነበር ሲሉ አስተያየታቸውን ደምድመዋል።

Tuesday, 20 October 2015

"መሰረታችን ሕገ መንግስቱ ነው" የወልቃይት ነዋሪዎች

ጥቅምት ፱ (ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ነዋሪዎች "መሰረታችን ሕገ መንግስቱ ነው ተብሎ የወልቃይት ነዋሪዎች ቋንቋን ብቻ መሰረት ያደረገና የሕዝቡን ስነ ልቦናዊ፣ ባሕላዊ ወግን ያላማከለና ያላጠቃለለ ክልላዊ አከላለል በማድረግ የወልቃይት ሕዝብ የማይፈልገውንና የማያምንበትን በመጫን በግድ ወደ ትግራይ እንድንካለል መደረጋችን በውስጣችን ያለውን ማንነታችንን በመጨፍለቅ እንድንቀበል እየተደረግን ነው ፣ዛሬ ስነ ልቦናችን የማይቀበለውን ሕወሃት በዘዴ ማንነታችንን ለማሸማቀቅ እየሞከሩ ነው" ብለዋል ። በማህበራዊ የመገናኝ ብዙሃን በተለቀቁ የስብሰባ ቪዴዮዎች ላይ አንድ ተናጋሪ ''እኛ እንደ ሲም ካርድ እኮ አይደለም አማርኛን የምንናገረው። በውስጣችን፣በደማችን፣በስጋችን በዘራችን ሁሉ የመጣ ቋንቋ፣የመጣ ባሕል፣የመጣ ስነ ልቦና ፣የመጣ ሕይወትና ኑሯችን ነው ያሉት ተናጋሪው፣ እኛነታችን ይበልጣል ታሪካችን ይበልጣል የአማራነታችን ጥያቄ በሕገ መንግስቱ ይፈታልን።'' ሲሉ ጠይቀዋል፡ ሁለተኛው ተናጋሪ በበኩላቸው ''ባሕላችን እየተረገጠ ነው።አንድ ብሔር ብሔረሰብ ማለት አንድ ዓይነት ቋንቋ፣ባሕል መልክዓምድር ያለው ይላል በዚህም ከአማራ ጋር ነው መሆን ያለብን።ቋንቋ መናገር ብቻውን ማንነቱን አይገልጽም።እኔ ነኝ አማራም ትግሬም መሆን መወሰን ያለብኝ በስነልቦና ስለተሳሰርን ወደ አማራ ክልል መካለል አለብን'' ብለዋል። "ሕገ መንግስቱ የፈቀደልን መብቶች ተጥሰው በቋንቋችን እንዳንጠቀም በግድ ተደርገናል የአማራነታችን ማንንነት በሕገ መንግስቱ ይፈታልን እኛነታችን እና ታሪካችን ይከበርል።ብዙ በደሎች ደርሶብናል፣ንብረቶች ተዘርፈውብናል፣ ዜጎች ተገለውብናል የደረሱብን በደሎች ይታዩልን" ሲሉ ሰቆቃቸውን አሰምተዋል። የወልቃይት ነዋሪዎች ችግራቸውን አስመልክተው ለፌደራል መንግስት ለትግራይ ክልልና ለአማራ ክልል ቢያመለክቱም እስካሁን ድረስ ሰሚ አለማግኘታቸው ነዋሪዎቹ ጠቁመው አሁን እስከመጨረሻው ድረስ በጥያቄያቸው እንደሚገፉት አሳስበዋል። ሌላ ተናጋሪ ደግሞ ነጻ የሆነ መድረክ ካገኘን እንናገራለን ካሉ በሁዋላ፣ ዛሬ አማራ ነኝ አማራነቴ ይከበር ብለዋል ይህ በማህበራዊ ሚዲያዎች የተሰራጨው ቪዲዮ መቼ እንደተቀረ የተገለጸ ነገር የለም ይሁን እንጅ ከቪዲዮው ለመረዳት የሚቻለው ቀረጻው በቅርብ ጊዜ የተካሄደ መሆኑን ነው።

በአዲስ አበባ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ የንግድ ተቋማት መታሸግ

ኢሳት ዜና (ጥቅምት በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ አሜሪካን ግቢ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ የንግድ ተቋማት ቦታው ለልማት ይፈለጋል ተብሎ ንብረታቸው መታሸጉን ነዋሪዎች ለኢሳት ገለጡ። የንግድ ተቋማት መታሸግን ተከትሎም የአካባቢው ነዋሪዎች መሰረታዊ የፍጆታ እቅርቦቶችን ለማግኘት ተቸግረው እንደሚገኙ የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት በሰጡት ቃለ-ምልልስ አስታውቀዋል። ወፍጮ ቤቶች ሱቆችና ምግብ ቤቶች ከታሸጉበት የንግድ ተቋመት መካከል እንደሚገኙበት የተናገሩት ነዋሪዎች የመንግስት አካላት የወሰዱት እርምጃ ተገቢ አለመሆኑን አስታውቀዋል። የንግድ ድርጅቶቻቸው ከመኖሪያ ቤታቸው ጋር ተያይዞ የነበሩት በርካታ ሰዎችም ማደሪያን አጥተው እንደሚገኙ ነዋሪዎቹ አክለው ገልጸዋል። ወደ አካባቢው ምንም አይነት ተሽከርካሪ እንዳይዘዋወር እገዳ ተጥሎ የሚገኝ ሲሆን፣ ነዋሪዎች ቅሬታቸውን የሚሰማላቸው አካል እንዳላገኙ ተናግረዋል። ተክለ ሀይማኖት እና ጃሊያ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ከታሸጉት የንግድ የንግድ ተቋማት በተጨማሪ በርካታ መኖሪያ ቤቶችም ይነሳሉ መባሉ በነዋሪዎች ዘንድ ስጋትን ፈጥሮ እንደሚገኝ ታውቋል።
የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ ለሁለተኛ ጊዜ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት አስመረቀ፡፡
አርበኞች ግንቦት 7 በሁለት ድርጅቶች ማለትም በኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር እና በግንቦት 7 ንቅናቄ ውህደት ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም ከተመሰረተ በኋላ ከትናትና በፊት እሁድ ዕለት ጥቅምት 7 ቀን 2008 ዓም ለሁለተኛ ጊዜ ብዛት ያላቸውን አርበኛ ታጋዮች ለሦስት ወራት አሰልጥኖ አስመርቋል፡፡
እነዚህ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሁለተኛ ዙር ተመራቂ አርበኛ ታጋዮች ለሦስት ተከታታይ ወራት የተሰጣቸውን የፖለቲካ፣ የወታደራዊ እና ሌሎች ተያያዥ የሆኑ የመረጃና ደህንነት ትምህርቶችን በሚገባ ወስደው በሁሉም መስክ አመርቂ ውጤት በማስመዝገብ ነው ሊመረቁ የቻሉት፡፡
እጅግ በጣም ደማቅ በሆነ ስነ-ስርዓት በተከናወነው የምረቃ በዓል ላይ ከተለያዩ ቦታዎች ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች የታደሙ ሲሆን የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ሊቀመንበር አርበኛ ታጋይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና የድርጅቱ የትምህርትና ስልጠና መምሪያ ኃላፊ አርበኛ ታጋይ ተስፋሁን ተገኝ ንግግር በማሰማት ለተመራቂ አርበኛ ታጋዮች መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ከውህደቱ ኋላ የመጀመሪያውን ዙር ሰልጣኞች ያስመረቀው ግንቦት 2 ቀን 2007 ዓ.ም መሆኑ ይታወቃል፡፡

Monday, 19 October 2015

ማማረር በቃ! መሰደድ በቃ! መቆዘም በቃ

ማማረር በቃ! መሰደድ በቃ! መቆዘም በቃ! ሀገራችን ኢትዮጵያ ከመቸውም ጊዜ በከፍተኛ ችግር ላይ መሆኗ ግልጽ ነው፡፡ ይህንን ስቃዩዋን እንድንታደጋት ዘወትር የጣእር ድምጿ፡- ‹‹….ልጆቼ ድረሱልኝ፤ አድኑኝ፤….ቦጫጨቁኝ፤ ከፋፈሉኝ፤ ገደሉኝ፤…..›› እያለች በማቃሰት ላይ ትገኛለች፡፡ የሰይጣን ውልዶች ሰይጣኖች እርሷንና ልጆቿን የተፈጥሮ ሀብቷን ደብዛ እያሳጡ ናቸው፡፡ ከአብራኳ የወጡት ጥቁር ፋሽስቶች ለማንነቷ ቁብ ሳይሰጡ እየረገጧት፤ እየመዘበሯት፤ እያስመዘበሯት፤ እየተቧጨቋት፤ እየከፋፈሏት፤….ድምጿ እንዳይሰማ ‹ሱቅ በይ› እያሉ እያደሟት ይገኛሉ፡፡ ይህንንም ለመታደግ እውነተኛና ቆራጥ ልጆቿ የጊዜ፤ የገንዘብ፣ የእውቀት፣ የአካል፣ የሕይወት፣….ወዘተ መስዋእት በመክፈል ላይ ናቸው፡፡ ይሁንና ኢትዮጵያ እናት ሀገራችን ሆና እያለች በ‹መታደግ› ሽፋን እንደሴተኛ ቅሬ ሊዳሯት የሚራኮቱ ደነዝ ባለጌዎች በኢትዮጵያችን ላይ ከማላገጣቸውም በላይ የልጆቿን እንቁ መስዋእትነት የሚያራክሱ፤ የሚያመክኑ፤…..የዘመናችን አሙካዎች ከምንም በላይ ልንፋለማቸው ግድ ነው፡፡ አወን እናት ሀገራችንን ከጭንቋ የሚታደጋት ንጥር ዜጋ እንጂ በግግር አስተሳሰቡ ሊገዛት፤ ሊነዳት፤ ሊዘርፋት፤ ሊቦጫጭቃት፤ ….የሚሻ የስልጣን አለሌ ጨርሶ እድል ልንሰጠው፤ በቸልታ ልናልፈው፤ ልንታገሰው፤ …ወዘተ. አይገባም፡፡ ከውጥኑ የዘር ፖለቲካ ያነገበ፤ በውስጥ አሸምቆ የጎጠኝነት ጭነት የተጫነ፤ የስልጣንና የጥቅም አስተሳሰብ አንግቦ የሚነሳን ማንኛውም ነገር ቁም! ረፍ! ወይድ!....ሊባል ግድ ነው፡፡ እምዬ ኢትዮጵያን በዘር፣ በጎሳ፣ በጎጥ፣ በብሔር፣ በሀብት፣ በእውቀት(በምእራባውያን)፣ በድንቁርና፣…በልዩ ልዩ የሀሳብ ክፍፍል እየፈረጁ የጭንቋን ጣእር የሚያራዝሙ፣ በዜጎች መስዋእትነት ለመሰልጠን የሚቋምጡ አሰሮችና ደነዞች ‹ዘረኝነትን እንታገላለን › እያሉ ጎጠኝነትን የሚያቀነቅኑ - ቅንጅትን፣ መኢአድን ባፍ ጢሙ የደፉትና በርካቶችን በሞትና በእስር እያስረመረሙ( ዘመነ ምኅረት፣ መለሰ መንገሻ፣ …ወዘተ.በቂልንጦ፤ አብርሐም ጌጡ(ላለፉት ሁለት ወራት በማዕከላዊ እስር ቤት ብቻውን በጨለማ ክፍል እየማቀቀ፣ ‘አርበኞች ግንቦት- 7 የምታደራጅ’ እየተባለ በከፋ ድብደባ እየተሰቃየ ያለና ከማንም እንዳይገናኝ ተከልክሎ በቅርብ ቤተሰቡ እንዲያዩት የተፈቀደ እንዲሁም ፍ/ ቤት የ28 ቀናት ቀነ ቀጠሮ እየተሰጠው የሚጉላላ)፣ ማሩ አሻገር፣..ወዘተ. በማእከላዊ የጨለማ እስር ቤት፣ ሌሎች ለቁጥር የሚታክቱ እስረኞችን ፍዳቸውን እያሳዩ) ከውጭ በሚላክ ፍርፋሪ የሰከሩ የሰሜን ሽዋ ግርድፎች፤ - ‹የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች› በሚል የተቆነፀለውና የወያኔ ስልጣን አራዛሚ የሆነው ፀጉራሙ መለስ(በየነ ጴጥሮስ)፣ - ከ‘ቅንጅት ተወክለናል’ በሚል ከወያኔ የተባረሩ ውልግዶችን በአመራር ያካተተው ‘አንድነት’ ብዙም ሳይጓዝ ሙሉ በሙሉ የወያኔ ገቢ ሆነ፤ - በፕሮፌሰር መራራ የመመራው ኦብኮ/ ኦህኮ በሚዲያ ከማነብነብ በስተቀር ያመጣው ፋይዳ የለም፤……ሌሎችም እንዲሁ፣…… ይሁንና የወያኔን ገመና በማጋለጥ የራሱ አወንታዊ ጎን ቢኖረውም በጭራሽ እንደወያኔ ላለ በዘርና በብሄር ፍጹም ለተዋሀደና ለገገረ ደነዝ ስብስብ በምንም የሚበጅም የሚፈይድም አይደለም፡፡ ሀገሪቱንስ ለወራሪ ሰጥቶ መቆዘምና መሰደድ ምን ሚሉት ጅልነት ነው??? ምክንያቱም ወያኔ ከራስ ተፈሪና ከኮ/ል መንግስቱ የከፋ አወዳደቅ በበለጠ እጅግ ተዋርዶ መልቀቅ ያለበት እንጅ እሽሩሩ በማለት በማባበልና በመማፀን የሚገኝ አንዳች ነገር ስለሌለ፡፡ በመሆኑም እነኚህ የዘመናችን ጭራቅ ሰይጣኖች በሚያደርጉት እኩይ ስራ በዝምታ፣ በቸልታ፣ በርቀት፣ በፍርሀት፣ ወይም በማበር፣ ወይም በልዩ ልዩ መንገድ በሚደርሰው ግፍና በደል ባይተዋር መሆን በምንም መልኩ፡- በትውልድ፣ በሕግ፣ ‘በኅሊና’፣ በጊዜ፣ በታሪክ፣…..ከመጠየቅ አይዳንም፡፡ ስለዚህ ሁሉም ዜጋ ኢትዮጵያዊ በሚችለው አቅም፣ የትም ቦታ፣ በአለው ችሎታና መሣርያ በተናጠል፣ በጋራ፣ በኅብረት፣ በአንድነት፣…ቆርጦ በመነሳት ወያኔንና ጀሌውን እንዲሁም የውጭ ተባባሪውን እገባ ግቢቱ ገብቶ ማጥፋት ልብ በሉ ማጥፋት አለብን!! ከመሰቃየት፣ ከመበላት ካልዳን ለምንድን ነው ራሳችን ቀድመን እማንበላው? ‘ጅብ ከሚበላህ በልተኸው ተቀደስ!’ አይደል የአበው ብሒል? ይህ ሲሆን ነው ሀገርን የምንታደግ፤ ይሕ ሲሆን ነው ሕዝብን የምንታደግ!! ይሕ ሲሆን ነው የዜግነታችንን ድርሻ የምንወጣ! ይሕ ሲሆን ነው የራሳችንን ችግር ምንከላው!! ሀገራችንን እናድን! እራሳችንን እናድን! ትውልድን እናድን! ሁሉም ለራሱ፤ በራሱ፤ በጋራ፤ በአንድነት፤…የአርበኝነትን ወኔ፣ መሣሪያ፣… ታጥቀን እንነሳ!!! ሀገር የሚናድን ከሀገር አዳኝ ጋር በኅብረት እንሰለፍ! ማማረር በቃ! መሰደድ በቃ! መቆዘም በቃ! ርትእ- ንጽሮት! አዲስ አበባ- ኢትዮጵያ

Saturday, 17 October 2015

ውሸት ውሎ አድሮ መጋለጡ አይቀርም!!!

ውሸት ውሎ አድሮ መጋለጡ አይቀርም!!!
Editorial PG7
ሥልጣንን በጠመንጃ አፈሙዝ ተቆጣጥሮ ያለው የወያኔ አገዛዝ ካለመታከት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ተአምር ሊመስል በሚችል መንገድ እያሳደኩ ነው እያለ ሲዋሽ አመታት ተቆጥረዋል። በተለይ ምዕራባዊያንን ሲያታልልበት የነበረው የዲሞክራሲ ጭንብል በምርጫ 97 ከተገፈፈበት ወዲህ ላለፉት አስር አመታት ባለ ሁለት አሃዝ እድገት አስመዝግቤያለሁ እያለ እጅ እጅ እስኪለን ድረስ በባዶ ሜዳ ስለ ልማትና የዕድገት ሲነግረን ሰነበቷል።
ወያኔ በጉልበት በሚያስተዳድራት ኢትዮጵያ የልማትና የእድገት ፕሮፓጋንዳ ስለ ሰበአዊ መብትና ስለዲሞክራሲ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለማፈኛና አፍ ለማዘጊያነት በማገልገል ላይ ይገኛል ። አለማቀፍ የሰባአዊ መብት ተቋማት ስለሰበአዊ መብት ጥሰት ለሚያቀርቡት አቤቱታ ሁሉ የሚሰጠው መልስ “ኢኮኖሚውን እያሳደግን ነው” የሚል ነው። ኢኮኖሚ ማደግ አለማደጉን ትርጉም የሚኖረው ከህዝብ የእለተ ተእለት ኑሮ ጋር ሲያያዝ መሆኑ ሁሉ ትርጉም አጥቷል። ራበኝ የሚለው ሰው ሁሉ ጠገብኩ ማለቱ ነው ተብሎም ይተረጎማል።
የውሸት ነገር ውሎ አድሮም ቢሆን መጋለጡ አይቀርምና ይኼው በቅርቡ የተከሰተው ድርቅ የወያኔን የውሸት ፕሮፓጋንዳ ክንብንብ ገፎታል። አለም በሙሉ አስር አመት ሙሉ በሁለት አሃዝ ሲያድግ የነበረ ኢኮኖሚ ባለበት ሃገር ውስጥ አንዲት የድርቅ አመት ካለርሃብና ልመና እንዴት መሻገር አቃተው የሚል ጥያቄ በሰፊው በማንሳት ላይ ነው። ወያኔ ለዚህ ጥያቄ መልስ የለውም። በአለም ዙሪያ ያለው ተመክሮ ሁሉ የሚያሳየው ወያኔ አድጌበታለሁ ብሎ ሲለፍፍ ከኖረው አሃዝ በታች በግማሽ ያደጉ ሃገሮች እንኳ አንድም ጊዜ አንድ የድርቅ ዘመን መሻገር አቅቶአቸው ሲንገዳገዱና መንግሥታቸው ለልመና ሲሄድ አለመታየቱን ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ ወያኔ የሚያወራውን ያህል ያልሆነ ቢሆንም በአንዳንድ ከተሞች አካባቢ የሚታየው እድገት የተገኘው ከውጭ መንግስታት የገንዘብ ብድር፣ በአለም አቀፍ ተቋማት እርዳታ፣ ስደተኛው ኢትዮጵያዊ በገፍ በሚልከው ገንዘብና ወያኔ ከድሃውና ከነጋዴው ከዝርፊያ ባላነሰ ሁኔታ በሚሰበሰበው ግብርና መዋጮ የተገኘ እንጂ ወያኔ ባስፋፋው ኢንዱስትሪና ልማት እንዲሁም ሀገር ውስጥ በፈጠረው ሀብት አለመሆኑ የሚታወቅ ነው።
የወያኔ ሹማምንትና አገልጋዮች ሀብት በሀብት መሆናቸውን እንደ እድገት ካልቆጠርን በስተቀር ህዝባችን ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮውን እንኳን መደጎም አልቻለም ።በዝርፊያ ገንዘብ ሹማምንቱና የወያኔ ባለምዋሎች የገነቡትን ፎቅ የሀገር ልማት ነው ካላልን በስተቀር እውነተኛና የህዝብ ህይወት ከመሰረቱ የሚቀይር ልማት አገር ውስጥ አለመካሄዱ ትንሽ ገለጥ ሲያደርጉት የሚታይ ሃቅ ነው። አንድ የድርቅ ወቅት መሻገር አቅቶት ብዙ ሚሊዮኖችን ከረሃብና እልቂት መታደግ ያልቻለ ኢኮኖሚ አስር አመት ሙሉ በሁለት አሃዝ አድጓል ብሎ የሚያምን ሰው ሊኖር አይችልም።
የወያኔ የኢኮኖሚ አሃዝ “መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ” ከሚለው የሀገራችን ግፈኛ አባባል ብዙም አይለይም። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለህዝብ በሚጠቅም መንገድ የማደጉ ጉዳይ በመጀመሪያ ፍትሐዊ ኢኮኖሚያዊ ሥርአት መገንባትንና ዴሞክራሲ ማስፈንን ይጠይቃል።
በመሆኑም የዛሬው የወያኔ ኢኮኖሚ የዝርፊያ ኢኮኖሚ እንጂ ህዝባዊ ሽታ የለውም። የኢትዮጵያን ህዝብ እዚህና እዚያ በሚብለጨለጩ ያውም በአብዛኛው በብድርና እርዳታ በተገኙ ልማት ተብዬ ነገሮች ለረዥም ጊዜ ማታለል አይቻልም።
ወያኔ በሚሰጠው አሃዝ የሚያድግ ማንኛውም ሀገር የውጭ ስደተኞችን ያስተናግድ እንደሆን እንጂ ወጣቶች ሞትና ህይወትን አማራጭ አድርገው አይሰደዱበትም። ባለ ሁለት አሃዝ አዳጊ ኢኮኖሚ በየትም ሀገር የስደተኞች ምንጭ ሆኖ ታይቶ አይታወቅም በዘረኛው ወያኔ ተገዢዋ ኢትዮጵያ ካልሆነ በስተቀር።
አርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ትንሳኤ ከዘራፊው የወያኔ ሥርዐት መወገድ ጋር በጥብቅ የተሳሰረ መሆኑን ያምናል! ስለዚህም ህዝባችን ወያኔን ለማስወገድ የተጀመረውን ትግል በነቂስ ለመቀላቀል ዛሬውኑ እንዲነሳና ከጎናችን እንዲሰለፍ የማያቋርጥ ጥሪውን ደግሞ ደጋግሞ ያስተላልፋል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!